.jpg)

.jpg)
.jpg)
.jpg)

መደበኛ ባልሆነ ፍልሰት ዙሪያ ከባለደርሻ አካላት ጋር ውይይት ተካሄደ ።
ደባርቅ ፡ - ሚያዝያ 06/2017 ዓ.ም (ሰሜን ጎንደር ኮሙዩኒኬሽን) የዞኑ ሥራና ሥልጠና መምሪያ ፍልሰትንና ስደትን አስመልክቶ በዞኑ ሥር ለሚገኙ የጥምረቱ የመምሪያ ኃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት በተገኙበት የ9 ወር አፈጻጸም ግምገማ አካሄዷል። ከወላይታ ሰዶ በተሻለ የፍልሰት አስተዳደር ከዩጋንዳ፣ ከደቡብ ክልልና ከሰዶ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ የተገኘውን ልምድ ለሰሜን ጎንደር ዞን የተሻለ የፍልሰት አስተዳደር ጥምረት ኮሚቴ አቅርቧል። የደባርቅ ከተማ የተሻለ የፍልሰት አስተዳደር የፕላት ፎርም ሰብሳቢ የኾኑት ወይዘሮ ሀብታም መንግሥቱ እንደተናገሩት ፕላት ፎርሙ ከተለያየ የማኅበረሰብ ክፍል የተወጣጡ 20 አባላት ያሉት ሲኾን በዋነት ግንዛቤ ፈጠራ ላይ እንዲሠሩ ተልእኮ ይዘው እየፈጸሙ እንደኾነ ገልጸዋል። በትምህርት ቤት ክበብ እንዲቋቋም አድርገዋል፤ በየመድረኩ እየተገኙ ግንዛቤ መፍጠራቸውንም ጠቅሰዋል። በበጎ ፈቃደኛነት የሚሠሩበት ዋናው ዓላማ ፍልሰቱ ምቹና ሕጋዊ ለማድረግ እንደኾነም ጨምረዋል። ከመንግሥት አካላትም ኾነ ከሌሎች አጋር አካላት በጥምረት ቢሠራ ውጤት ይመዘገባል የሚል አስተያየት ሰጥተዋል። እውቅና ያገኘ ማኅበር በመኾኑም ቋሚ የኾነ ቢሮ እንዲመቻችላቸው ጠይቀዋል። በአንፕካን ኢትዮጵያ ደባርቅ ቅርንጫፍ የተሻለ የፍልሰት አስተዳደር (Better Migration Management) አስተባባሪ አቶ ሲሳይ ብርሃኔ ፕሮጀክቱ በበርካታ ማኅበራዊ ጉዳዮች በተለይም በጤናው፣ በሰላምና በሕገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር ዙሪያ ትኩረት አድርጎ እየሠራ ይገኛል ብለዋል። ይህን ትኩረት በማድረግ የጥምረቱ አባላት የ9 ወሩን አፈጻጸም መገምገሙን አድንቀው ለፕላት ፎርም አባላት/ለበጎ ፈቃደኞች/ ትብብር ማድረግ እንደሚገባ አሳስበዋል። የሰሜን ጎንደር ዞን ሥራና ሥልጠና መምሪያ ምክትል ኃላፊ አቶ ደገፋው ታከለ የቀረበውን ሪፖርት የተሻለ እንደኾነ አንስተው በቀጣይ የጎደለውን በውይይትና በተግባር ሥራ በመሙላት ማኅበረሰቡ ከሕገ-ወጥ ፍልሰት ራሱን እንዲጠብቅ ባለድርሻ አካሉ ተገቢውን ተኩረት እንዲሰጥ አሳስበዋል። የማኅበረሰቡ ግንዛቤ ሊያድግ የሚችልበትን አማራጭ መጠቀም እንዲሁም ከሕጋዊ የሥራ ሥምሪት አኳያ መግባባት የሁሉም ተቋም ኃላፊነት መኾኑንም አክለዋል። የስደት ተመላሾች ከይስሙላ ያለፈ መልሶ ማቋቋም ላይ ትኩረት መስጠት እንደሚገባም ጨምረው ተናግረዋል ። የዞኑ ፍትህ መምሪያ ኃላፊና የጥምረቱ ሰብሳቢ አቶ ነጋ ሲሳይ የእንደ መንግሥት፣ እንደ ፕላት ፎርምና እንደ በጎ ፈቃድ ማኅበር መሥራት በሚገባ ጉዳይ ላይ ሐሳብ ሰጥተዋል። በዞኑ ሁሉም ወረዳዎች የዞኑን ጥምረት ተከትለው መደበኛ ባልሆነ ፍልሰቱ ዙሪያ መሠራት እንዳለበት አብራርተዋል ። መደበኛ ያልሆነ ፍልሰትና ስደት የመቀነስ እንቅስቃሴ ዙሪያ ደባርቅ ከተማን ለዞኑ ወረዳዎች የተሞክሮ ማእከል እንዲኾን መሥራት ይጠበቃል ብለዋል። በፕሮጀክቶች እየተገፋ የሚሠራ መዋቅር መኖር የለበትም ያሉት የፍትህ መምሪያ ኃላፊው ከእያንዳንዱ ተቋም የሚጠበቀውን ግዴታ መወጣት እንዳለበት ተናግረዋል። የማኅበረሰብ ሬዲዮ በዞኑ ማቋቋም ቢቻል የሚል ከፍ ያለ ሀሳብ አቅርበዋል። መደበኛ ያልሆነ ፍልሰትን በመከላከል በኩልና ስደት ተመላሾችን፣ ከአቀራረብ ከአያያዝና ከአገልግሎት አሰጣጥ አንጻር በባለቤትነት መሥራት እንደሚገባም አሳስበዋል።