





የእንስሳት ዝርያን በማሻሻል ማኅበረሰቡን የወተት ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ እንደሆነ ተገለጸ።
ደባርቅ ፡ - የካቲት14/2018 ዓ.ም (ሰሜን ጎንደር ኮሙዩኒኬሽን)
በወረዳና በከተማ አስተዳደሮች የእንስሳትዝርያዎችን በማሻሻል ከ15ሺህ 400 በላይ ቶን ወተት ለተጠቃሚው ማድረስ መቻሉን ዞኑ እንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት መምሪያ አስታውቋል።
የዞኑ እንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ሸጋው ጌታቸው የተሻለ የወተት ምርት ለማግኘት ዝርያ በማሻሻል ወደ 20 ሺህ የሚደርስ እቅድ የተያዘ ቢኾንም ከ4ሺ 100 በላይ በሦስቱ የዝርያ ማሻሻል ሥርዓት እየተሠራ እንደኾነ ገልጸዋል። የዝርያ ማሻሻልን ሥራ ለመከወን የናይትሮጅኖና አባላዘር ከጎንደር ስለሚመጣ በጸጥታው ምክንያት ውጤቱ ዝቅ ማለቱን ተናግረዋል። በደባርቅ ከተማ በቀን ከ100 ሊትር በላይ ወተት የሚያገኙ የወተት ላሞች ባለቤት መኖራቸውንም ጠቅሰዋል።
የወተት ማኅበር ለማቋቋም መረጃዎች እየተሰበሰቡ እንደኾነ የገለጹት ኃላፊው ወተትን በጾም ሰዐት ብክነት እንዳይገጥመው በማቆያ ዘዴ በወተት ፋብሪካ ተጠቅመው በየሱቁ የሚሸጥበትን እሴት እንፈጥራለን ብለዋል። በወተት ምርት የተሰማሩ ግለሰቦች ከ2 ላም ወጥተው ከ10 በላይ ቢያሳድጉ የተሻለ የማርቢያ ቦታ በግብርና በኩል እየተመቻቸላቸው መኾኑንም ጠቁመዋል።
በደባርቅ ከተማ በአንዲት ላም ወተት ምርት የጀመረው ወጣት ፍቃዱ ተሰፋሁን ዘርፉ አዋጭ በመኾኑ አሁን ወደ አራት እንደደረሱ አንስቷል። የወተት ፋብሪካ አለመኖሩ ኪሳራ እየደረሰባቸው እንደኾነ ገልጿል። ሌላው የአባለዘር እጥረት መኖሩን የጠቆመው ወጣት ፍቃዱ ለማዳቀል በፈለገ ጊዜ እንደማያገኝ ነው ያብራራው። ውጤታማ የወተት ምርት የእንዲኖር ከከተማ አስተዳደርም ኾነ ከዞን የባለሙያ ድጋፍ እየተደረገላቸው እንደኾነ ተናግሯል። ለዘርፉ ያለውን ፍቅር በመግለጽ በሥሩ ለአራት ወጣቶች የሥራ እድል እንደፈጠረ አክሏል።
ሌላኛው በደባርቅ ከተማ በወተት ምርት የተሰማራችው ወጣት ችሎት ሰጠኝ ሥራ ሳይንቁ በመሥራታቸው ከምንም ተነስተው የሀብት ባለቤት መኾናቸውን ተናግራለች። የመኖ አቅርቦት፣ የወተት የገበያ ትስስርና ብድር ቢመቻችልን የሚል አስተያየት አቅርባለች።